
By Admin
ለውንብድናም ባይሆን ለውትድርና፤ ለወንበዴም ባይሆን ለወታደር ትልቅ ክብር አለኝ። ውትድርና ለእኔ፦ ዓይን የሚያየው አቅም እና ጉልበቱ ውስን የሆነው የሰው ልጅ፡ የማይደማ የማይቆስለውን፣ ስውር እና ጨካኝ የሆነውን የሞት መላዕክት በድፍረት የሚጋፈጥበት ክቡር ሙያ ነው። ወታደር ደግሞ ሞቶ የሚያኖር ደፋር ፍጡር። እንደ ዕድል ሆኖ ለውትድርና ሙያ ስልት እና ብልሃት መሀይም ነኝ። ነገር ግን የወታደርን ውሎ እና ገድል ማዳመጥ ዛሬም ድረስ ደሜን ያሞቀዋል።
ወያኔ እንደዛሬው ደርቆ፣ ጥርስ አውጥቶና ሰይጥኖ ነፍስ መብላት ሳይጀምር፤ ያኔ ገና ከተማ እንደገባ፣ ለጋ እርጥብ እንዳለ፡ አንጀት እና ልብ ለመብላት ሲዳዳ፡ በየመንገዱ እና በየሰፈሩ ያሳዩን የነበረው መልካምነት ጆሮአችንን እንድንሰጣቸው አስገድዶን ነበር። እንደዛሬው መሰብሰባችን ለደህንነታቸው ስጋት ሆኖ በጅምላ እየፈጁ ወደ መቃብር ሳያወርዱን፡ ድሮ መሰብሰባችን ለደህንነታችን አስግቷቸው “ከተማው ሰላልጠራ ደርግ-ኢሰፓ ለእኛ የምትተኩሰው ጥይት፣ የምትወረዉረዉ ቦምብ እናንተን ሊጎዳችሁ ይችላል” ብለው በፍቅር ወደየቤታችን ይሽኙን በነበረበት ጊዜ፤ በየአጋጣሚው የምናገኛቸውን “ተጋዳላይ” ወያኔዎች ለመታዘብ ተሰብስበን ከበናችው ስንዉል፡ በኩራት ይተርኩልን የነበረውን የውጊያ ስልት (ስትራቴጂ) ዛሬም ድረስ አስታውሰዋለሁ ፦ቆረጣ!
ቆረጣ ምን እንደሚመስል በተግባር ሜዳ ላይ ወይንም ደግሞ በተውኔት መድረክ ላይ ለማየት ባልታደለም፡ ከጀሌዎቹ አፍ ያዳመጥኩትን የተሰባበረ የአማርኛ ወግ ገጣጥሜ ስዕላዊ ምናብ ለማግኘት ግን አልተቸገርኩም። አንድ ወጥ የሆነን ሠራዊት ቢቻል ብዙ ቦታ ካልተቻለም ደግሞ ቢያንስ ሁለት ቦታ ከፈሎ፣ ጉልበት አሳጥቶ ማጥቃት።
ወያኔ ሜዳ ላይ ግዙፉን የደርግ ሻለቃ እና ብርጌድ በዳዴ አስኬድኩበት ብሎ የሚመጻደቅበትን፣ የግሌ የሚለውን የጦር ሜዳ ቆረጣ፡ ዛሬም በከተማው የሰላማዊ ትግል ውጊያ ላይ የተካነበት መስሎ መታየት ጀምሯል። በተለይ በጎጥ እና በሀይማኖት ተደራጀተው በሚከወኑ እንቅስቃሴዎች ውስጥ።
ነገር ግን ሰላማዊ ሰለፉ በተጓዳኝ ምን ፍላጎት እና አላማ ነበረው? እነማን ሾፈሩት? እነማንስ በቆረጣ ስልት ተሳፈሩት? የሚለውንም በጥሞና መመልከት ከተመሳሳይ ሀዘን ይታደገናል ብዪ አምናለሁ።
የኦሮሞ ተወላጅ ተማሪዎችን ሰልፍ ተታኮ በድህረ ገፅ ላይ የምናነባችው፣ በመገናኛ ብዙሃን ላይ የምናደምጣቸው፡ ከአዲስ አበባ አካባቢ ገበሬዎች መፈናቀል ጋር ዝምድናም ሆነ ጉርብትና የሌላቸው ፀረ-አማራ፣ ፀረ-ኦርቶዶክስ፣ ፀረ-አፄ ምንሊክ አመለካከቶች እና መፈክሮች የማን ናቸው? የኦሮሞ ተወላጅ የሆኑት ተማሪዎች? ወይንስ የቆረጣው ቅጥረኞች?
ለየትኛውም ዘር ወይንም ሃይማኖት መብት በተናጥል የሚንቀሳቀስን ሰላማዊ ትግል በቆረጣ ማጥቃት ለወያኔ አይከብድም። አንድነትን ያላማከለ የመብት ጥያቄ የቱንም ያህል እውነታ እና አግባብነት ያለው መስሎ ቢታይም፡ ወያኔ “የራሴ” የሚላቸውን – የኣንድን ጓሳ ባህል እና ቋንቋ በደም የተዋሃዱ አሊያም በስም የተላበሱ ቅጥረኞችን በቆረጣ አቀላቅሎ፡ ዓላማን ለማጣመም፣ ጩኸትን ለማፈን ችግር አይኖርበትም። ምክንያቱም፦ በጓጥ ተከፋፍሎ የወጣ ለቆረጣ ይመቻልና።
የውጊያ ስልት የሆነውን “ቆረጣ“ በኢ-ሰብአዊ “ግድያ” ቃል ብንተረጉመው እንኳ፡ በዘር ተደራጅቶ ጓጠኝነትን ለማንገስ በወጣ ማህበረስብ ላይ ስለሌላው ብሔረሰብ ደህንነትና ጥበቃ ሲባል የሀይል እርምጃ ፈጽምኩ ብሎ፡ መራር እውነታን በጣፋጭ ውሽት እንዲዋጥ ለማስገደድ አይከብድም። ለዚህም ነው በሁለተኛ ትርጉሙ፡ በጓጥ የሚወጣ … ይመቻል ለቆረጣ ( ለግድያ) ያልኩት።
አዲሱን የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር ማስተር ፕላን በመቃወም የተሰለፉት ወጣቶች፡ የከፈተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች አንጂ የአፀደ-ህፃናት መዋያ ጨቅላዎች አይደሉም። ክፉና ደጉን በጅምላ መለየት ብቻ ሳይሆን፡ ክፋትንም ሆነ ደግነትን ከፋፍሎ በደረጃ ለማስቀመጥ የሚያሰችል በሳል አእምሮ ያላቸው ጎልማሶች ናቸው። አሁንም ቢሆን፦ ዓላማቸውንም ሆነ ህልማቸውን፣ መነሻቸውንም ሆነ መድረሻቸውን፣ አስተባባሪዎቻቸውንም ሆነ ተባባሪዎቻቸውን በከፈተኛ ጥንቃቄ ማሰተዋል ይገባቸዋል። የተፈናቃይ ገበሬዎችም ሆነ ነዋሪዎች ደህንነትና የወደፊት ዕጣ-ፈንታ፡ የመላው ኢትዮጵያ ተማሪዎች ጥያቄና ግዴታ እንጂ፡ የኦሮሞ ወይንም የአንድ ጓሳ ብቻ ተድርጎ መወሰድ የለበትም። የአዲስ አበባን መስፋት ከአማራው ብሔረሰብ መስፋፋት ጋር አቆራኝቶ ደም ለመፋሰስ መውጣት፡ ለወያኔ ቆረጣ ከመመቸት ባሻገር የተማሪዎቹን ጥያቄና ፍላጎት ግምት ውስጥ የሚያስገባ ነው።
የፋሺስት ገነት ዘውዴን አስተዳደር ተከትሎ፡ የወያኔ የዘር ፖለቲካ በትምህርት ተቋማት፡ በተለይም በኮሌጅ እና በዩኒቨርሲቲ የካምፓስ ህይወት ውስጥ ምን እንደሚመስል ለማወቅ ነጋሪ የሚያስፈልገን አይመስለኝም፡ ሁላችንም አልፈንበታልና። ከማደሪያ ዶርምተሪ አንስቶ እስከ መመገቢያ ጠረፔዛ መለየት ድረስ፡ ጎጠኝነት፦ ፋከልቲ እና ዲፓርትመንት ሳይለይበት – ከሰኞ እስከ እሁድ በሰባት ክሬዲት ሃወር (credit hour) የሚሠጥ ኮመን ኮርስ (common course) ቢሆንም፡ መውደቅም ሆነ ማለፍ ግን በኢንስትራክተሩ (በአስተማሪው) ሳይሆን በራሱ በተማሪው መመዘኛ የሚወሰን ነው። መከፋፈልን በህብረት፣ መለያየትን በአንድነት አጣፍቶ ለማለፍ ደግሞ ተማሪው ብቁ የስሌት ዕውቀት ያለው ይመስለኛል። የከፍተኛ ትምህርት ተቋም በር እንደ መርፌ ቀዳዳ በጠበበበት ምድር ሾልኮ ገብቶ እራሱን የዩኒቨርሲቲ ተማሪ ያደረገ ዜጋ፣ በምናባዊ ሳይንስ እና ፍልስፍና “ጢባ-ጢቢ” የሚጫወት ጭንቅላት፡ ነባራዊ ታሪክን ለመረዳት ብስለት ይጎለዋል የሚል ግምት የለኝም። ሰለዚህ፦ የኦሮሞ ብሔረሰብ ተማሪዎች፡ ለለውጥም ይሁን ለነውጥ አንድነት ሀይል መሆኑን ተገንዝበው፡ ከሌሎች ተማሪዎች ጋር በመተባበር ፍላጎታቸውን ከተዛባ ትርጉም አፅድተው – በኣንድ ድምፅ፣ በኣንድ ሃይል፣ ለኣንድ አላማ በመሰለፍ ራሳቸውንም ሆነ ጥያቄያቸውን ከቆረጣ (ከነፍስ ግድያ እና ከአላማ ቅልበሳ) በጋራ ሊከላከሉ ይገባል እላለሁ።
እኔ በግሌ፡ ከጥቂት ወራት ወዲህ በሃገሪቱዋ ውስጥ እየሰፋ በመጣው የጎሳ ጥላቻ ለሚጠፋው ነፍስም ሆነ ለሚወደመው ንብረት፡ ከጄነራሉ ወያኔ እኩል ከሃገር ውጭ ተቀምጠው ዘመቻውን በስካይ-ፒ እየመሩ ያሉትን ኣስር-አለቆች ተጠያቂ አደርጋለሁ። በዱላ እና በገጀራ ተደብደቦ ለጠፋው የአዛውንት አማራ ገበሬ ህይወትም ሆነ በግፍ በአደባባይ ለተጨፈጨው የኦሮሞ ተማሪዎች ነፍስ፣ ከሰው በላው ኣጋዚ እኩል፡ የጥፋት እሳቱን ለማንደድ ኣጋዥ ሆነው ሰፊ አፋቸውን እንደ ወናፍ እየተጠቀሙ ያሉት የዲያስፖራው ፖለቲከኞችም ሃላፊነት ሊወሰዱ ይገባል።
በሃገር ወስጥ የሚፈሰው ንጹህና ክቡር የኦሮሞ ህዝብ ደም በውጭ ሃገር ለሚኖሩ ጥቂት ተወላጆች ነን ባይ ጎጠኞች፡ የጥገኝነት ጥያቄቸውን አለበለዚያም ስምና ዝናቸውን የሚያደምቁበት ርካሽ ቀለም ነው። ጥቂቶች በባዕድ ምድር ተንደላቀው ለመኖር፡ ብዙሀኑ ደሃ በትውልድ ሀገሩ በግፍ ተጨፍጭፎ ማለቅ አለበት። ያኔ ነው የቅርብ እና አዳዲስ መረጃ (recent and new facts) የሚለውን የየሃገራቱን የስደተኞች ቢሮ መመዘኛ ጥያቄን በአባሪ ድብዳቤ በብቃት መመለስ የሚቻለው። ያኔ ነው ሰላማዊ ሰልፍ ጠርቶ መሪ የመሆንን የዘመናት የጓዳ-ህልም ለደቂቃም ቢሆን በአደባባይ መኖር የሚቻለው። ያኔ ነው “ለጉዳተኞች መቋቋሚያ“፣ “ለተራፊዎች መከላከያ” በሚል ሰበብ ጨዋታው ካልገባው የዋህ ተወላጅ ገንዘብና ንብረት በሀራጅ መንጠቅ የሚቻለው። የደሃው ሞት ለእነሱ ትንሳዔ፣ የደሃው መርገመት ለእነሱ በረከት ነው። እነዚህ በጣም ጥቂት፡ በኣስር እና ሃያ የሚቆጠሩ የዘር ዛር የሚጋልባቸው የፍቅር መካን በቅሎዎች – “በእኛ ይብቃ” የሚል ቀና መንፈስ ያላቸው ዲያስፖራዎች ሳይሆኑ፡ ደም እንደ ካባ የሚያደምቃቸው ዲያብሎሶች ናቸው። ከራሳቸው አስቀድመው ለመጪው ትውልድ ከማሰብ ይልቅ – “እኔ ያልኖርኩበትን ሰላምና ፍቅር ሌላው ሊያየው አይገባም” የሚል ሰይጣናዊ ቅናት የሚንጣቸው።
ከእዚህ ባሻገር ግን፡ በጓጥ ተደራጅቶ “ለምን አትከተለኝም?“, “እኔ ስሰለፍ አንተ ለምን ትማራለህ?” ብሎ መጠየቅ፡ በአቡኑ ቋንቋ “መናፍቅነት” ነው። የኢትዮዽያን ህዝብ ወክዪ ለመናገር ባልደፍርም፡ እኔና የእኔ የሆኑት፣ እኛንም የመሰሉት ግን ከሌላው ኢትዮዽያዊ ኦሮሞ ጋር በጋራ ለሃገር ጥቅም የምናፈሰው ኢትዮዽያዊ ደም እንጂ፡ ለመንደር የሚሆን ጠብታ ጓጣዊ የውሃ ላብ የለንም፤ አይኖረንምም። እኔና የእኔ የሆኑት፣ እኛንም የመሰሉት ግን፡ ከሌላው ኢትዮዽያዊ ኦሮሞ ጋር በጋራ ለአንዲት ኢትዮዽያ የምንሰዋት አንዲት እና ብቸኛ ህይወት እንጂ፡ ከውጭ ሃገር በተልዕኮ የሚሰበከውን የጓጠኝነት ጥላቻ ለሚያቀነቅን በቀቀን በረከት የሚሆን ትርፍ ነፍስ የለንም፤ አይኖረንምም።
የኣንድ ወገን ብቻ ፍቅር እና ትዕግስት ለዘመናት ሲሰበክ፡ ትውልድ የማይዋኘው ወንዝ፣ የማይወጣው ገድል ውስጥ ተወርውሮ አልቋል። ችሎ-አዳሪነት እንደ አድሃሪው ስርዓት ላይመለስ አልፏል። ዘረኝነት የሥነ-አእምሮ ህመም ነው – ዕብደት! ዕብድ ደግሞ ይሻለዋል እንጂ አይድንም። ዛሬ በአጉል ሆደ-ሰፊነት ሸፍነን እና አለባብሰን የምንኖረውን ጥላቻ ሳይሆን፣ በድፍረት ገልጠን እና ተጋፍጠን፡ አስፈላጊም ሲሆን ተጣፍተን የምንሞተውን ፍቅር መርጠናል። እኔና የእኔ የሆኑት፣ እኛንም የመሰሉት ለመጪው ትውልድ ልናቆየው ቃልኪዳን የገባነው፦ የሚያስነክሰውን ያመረቀዘ ቁስል ሳይሆን፡ የሚያሰተምረውን የዳነ ጠባሳ ነው።