Post

ታሪከኛው ግንቦት

By Admin

የቀን  ተረኛው  ነፍስ … ሲዋከብ  አርፍዶ
ወዲህ ሲል ፡ ወዲያ  ሲል … ግሎ  ላቡን  ማግዶ
ጀንበር  በጨረቃ … በፅልመት  ተሳዶ
አውሬ፣  ጂኒ  ሲነግስ … ደጅ  ቀፎ፣  ደጅ  ከብዶ

በድካም  ሲባጎ … እንቅልፍ  ተቀስታ
የብርሃን  ፍጡር … ቆስሎ  በሽልብታ
ምድር  እረጭ  ብላ … ሰማይ  ኮከብ  ለብሶ
ዥጉርጉር  ወገኛው … አፈር  ህዝብ  ተማ
በእፎይታ  ድባብ … ድፍርስ  አይኑን  ከድኖ

ማልዶ  እስኪነቃ … ዳግም  ለህይወት  ፍልሚያ
ሲያስታምም  ትክተቱን … በትራስ  ላይ  ኩርፊያ

ላየው  ተአምር  ሲያሰኝ … ሯጭ፣  ተወንጫፊ  ስጋ
በአንሶላ  ላይ  ሰክኖ … ተዘርሮ  በአልጋ፤

ለካስ …
በማሾ፣  በሻማው … በአዳም  ጥበብ  ር’ቀት
በአምፑል፣  በፋኖሱ … በሰው  ሳይንስ  ምጥቀት
ንግሰት  መከልከሉ … ግርማ  መቀማቱ
ቆሽቱን  አሳርሮት … ሲከስል  ኖሮ  አንጀቱ

ያረገዘውን  ቂም … ሊሸከም  ተስኖት
ምሽት  ሲያምጥ  እሳት … ሊገላገል  ወልዶት፦

ሳትዳረስ  ንጋት  ምደሪቱን  ሊያፈካት … በእግዞይታ  ወ’ይኔ
ሲተፋው  እሳቱን  ሊያነፍረው  ጥሬውን … ግሞ  ለብሶ  ወኔ
ጢሽ!ም  በስሎ  በፍም … እስኪሰማ  ዷ!  ድው!  ግምምም!
ነበልባል  ለብልቦት  የጥይት  ኡኡታ … እስኪቀልጥ፣  እስኪግም

በ “እንዲህ  ነበር  ያኔም ” … ፍጡር  ተጃጀሎ
ንቃት፣  ጥንቃቄ … በወቅት  ሸማ  ታ’ጅሎ

ተማግዶ  ቤት፣  አጥሩ … አረር  ሲፈናጠር
እግር  አልባው  እሳት … እንደ  ንስር  ሲበር
ነገር  ካበቃለት … ጀምሮ  መጠርጠር

ንቃትን  ጨርፎ … ገሚስ  እሱነቱ  በሰመመን  ታብቶ
ድንብር  ግትር  ሲል … በደመ-ነፍስ  ሩጫ  ፍጡር  ዋሻ  ሽቶ
ስንት  ጉድ  አሳየን … ልንስቅ፣  ልናለቅስ
የበቅሎው  ቤት  እሳት … የግንቦቱ  ድግስ

የሽብር  ጥቁር  ከል … ብሩህ  አእምሮን  ጋርዳ
ፆታ፣  ርህራሄ … ጠፍተው  በየተራ
ታይቷን  ነጥቆ  ከሚስት … ድንጉጥ  አባወራ
አስገብቶት  ቀኙን … ሲጠበው  ለግራ
ሲገፍ  የውስጥ  ልብስ … አቤት!  የጭንቅ  ሥራ …

ባርኔጣ  ስትጎትት … መነፅር  ላይጠቅማት
እንደ  ስካርቭ  ጠምጥማው … የባሏን  ክራቫት
እንዳልተዋቀረው … አጥንት  እንደሌላት
እግሯ  አልቆም  ብሎ … እማወራ  ጨንቋት
ስትሳብ  በምድር … እንሽላሊት  አርጓት …

አቤት!  አቤት!  አሉ … አያቴ  አቤት!  አቤት!
በጣር፣  በአውጪኝ  ነፍስ … ሲውተረተር  ፍጥረት
ታሪከኛው  ግንቦት … ስንቱን  አየንበት

በእሳቱ  ኮማንዶ … በአረሩ  ፋኖ
እግሩ  ሙዚቀኛ … አይኑ  የእውር  ሆኖ
በረንዳ  ላይ  ቆሞ … እንዳይሮጥ  ዕርቃኑን
የሃያው  ጎረምሳ … ሲያማርር  እድገቱን
ሲመኝ  ጨቅላነቱን…

እራፊ  “ሆት፡ፓንት”ዋን … ብቻ  እንደታጠቀች
ከወገብዋ  በላይ … እንደተፈጠረች
ጉች፣  ጉች  አንዳለች
ብቅ  ስትል  ቢያያት … እጆችዋን  አጣምራ
አካሏን  ልትደብቅ … እህት-ዓለም  አፍራ፦

ሳይዘፍኑ  ደናሹን … ገላውን  አርቆ
ዘሎ  ወደ  እህቱ … ወገቧን  ተጣብቆ
ከሰጠችው  ታጥቆ … ሊጠፋ፣  ሊመንን
በእናት፣  በአባታቸው … በኣርባ-አራቱ   ታቦት  ሲገዝት፣ ሲለምን

እሷም  ልትራራለት … ልትሆነው  ያቺን  ቀን
አሻፈረኝ  ብላ … ፍጹም  ብትለመን
በኣስር  ጣቷ  ስትስብ … ስትገፋ  ወደ  ላይ
እሱም  ሲተናነቅ … ቁልቁሉን  ከእጇ ላይ
በርትቶ  ጎትቶ  ቢያደርሰው  ከምድር … ሞት  የሞቱን  ስቦ
ትግሉ  አንዳይማረር  ሊሸመግል  ሊዳኝ … ይመስል  አስቦ
ፍንዳታው  ቢያቀልጠው … አርገፍጋፊ  ድምፁን  በብርሃን  አጅቦ

እርሱም  ሳይታጠቅ … እርሷም  እዛው  ጥላው
ለአንዳቸውም  ሳይሆን … መከረኛ  ቁምጣው
እርቃኑን  ሲከንፍ … ጭንቀት  አስደንብራው
በዋይታ  እያጀበች … እህቱም  ከኋላው
ከተረፉም  ከእሳት … ስጋችው  ሊታኘክ፣  የሰው  አይን  ሊበላው
ቀድሟት  ከደጅ  ወጣ … አልቀረም  የፈራው፤

ፍጡር  መተንፈሱ … ህልወናው  ልሞ
ህመምተኛ  ድኖ … ጤነኛም  ሰው  ታሞ
ሴተ-ላጤ  ቅርሷን … አባወራም  ሚስቱን  እንደ  ጉድፍ  ጥሎ
ነፍስ  እየመዘነች … ከሜዳ  ሲተን፣ ሲፈስ  እንደ  ቆሎ

እንደ  “እሳት-አደጋ” … አባ-ዲና፣  መርማሪ
ከጭንቅ  መንደር  ውሎ … የደላው  ሰርሳሪ
በአንድ  ጀንበር  አጥቦ … የደንባሬን  ጉያ
ሳይመርጥ  የጠመመ … የዛገ  ማጥለያ
ተሸክሞ  ሲሮጥ … አሸክሞ  አህያ …

ታሪከኛው   ግንቦት
ሰንቱን   አየንበት!

ተራፊ  ሲያለምህ … ትርፈቱን  አድንቆ
ወፈፍ  ያደረገው … በላንቃህ  ነበልባል፣  በሽብር  ሸብርኮ
ዛሬ  ሲያስታውህ … የብርክ፣ ምጡን  ግግር  ከእላዩ  ፈቅፍቆ
ስንቱ  ይፈግ  ይሆን … የታሪክ  ድራማ  ድርሰትህን  አድንቆ?

ስንቱስ  አቄመብህ … ሊያስብህ  በእንባ  ታድሎት  ሰቆቃ
እሳትህ  አላምጣ … ፍርግርግ  ምሰሶ፣  ማገሩን  አድቅቃ
ያስጠላችው  ሸራ … ጣሪያ  ቆርቆሮውን፣  የአፈር  ምርጉን  ነጥቃ?

በወቅቱ፥ መታሰቢያነቱ ለበቅሎ ቤት ጉዳተኞች የተሰጠ።
(*የአፈር ምርግ = ስጋ = የሰው አካል)

1983 ዓ.ም.

Comments are closed.