Post

አኳኩሉ  ሲባል … ነግቷልን  ብታወቂ

አኳኩሉ ሲባል … ነግቷልን ብታወቂ

ጥቅምት  የወጋውን … ግንቦት  ላይ  ቢነቅለው
ለሊት  የማሰውን … አድሮ  ቢሸፍነው
ስሙ  ቢቀያየር … መልክ፣  ልኩን  ላንስተው
እሱው  እራሱ፦ ይኼው!

ተመርዞ  ላይድን … በስብሶ  አናቱ
ቀኝ  እጁ  ከግራው …  ምን  ነው  ልዩነቱ
ከርሞ  የሚያኮራሽ … ተስፋ፣  ጤንነቱ
ኢምንት  ደህንነቱ?
 
ጠኔ  ጠፋ  ችግር … ሰላም  ነው  የሚልሽ
ሲያባብልሽ  አንጂ … አቁስሎ  ሲልስሽ
የልጅ  ውርጃ … ያ  ዲቃላሽ
ጥምል፣  የካብ  ስር  ላሽ!

ክህደት  ነበረ … ለእናትነት  ምስሽ?
 
በያ  ተጠየቂኝ … እስቲ  እውነታ  ካለሽ
አሁን  ነው  ወይያኔ … የሚሆን  ከለላሽ
ገፎ  የሚያራቁት  … ሸማውን  ከገላሽ
ሽፋንሽን ከላይሽ?

በዳር፣  በገጠሩ… ጥፋትን  ሲያባዝት
እጁ  ሲያወጣ  ቅርስ … ሳንጃው  ሲያወርድ  ቅሪት
እግዞዞዞ!  አንዳላልሽ … ጆሮሽ  ቀፎት
ስብሀት  ለሞት!
 
ግንባርሽ  ባቋረው … የድካም  ላብ  ውሃ
ማሳ  ሲያሸት  ከርሞ … በሱዳን፣  ሊቢያ
ከእዛ ቅጥር … ያኔ፥ ወዲያ
የዘር ትቢያ!

ስናውቅ  ማንነቱን … ሳይርቅ  ትላንትና
ዛሬ  ቢያዜም  ደርሶ … በይሁዳ  ቃና
ሊያሳየን  ታምራት … ሰላም፣  ብልፅግና
የቀበሮ ባህታ

እንዴት  ”በጄ”  አልሽዉ … የአስቆርቱን  ድቁና?
 
በያ  መልሺልኝ … ይታወቅ  ምክንያቱ
ከጀግና  ተዋልደሽ … በዝቶ  ዘር፣  ማንዘሩ
ኣንድ  ልጅ  የጠፋው … ሲባል  “አኳኩሉ
”ነግቷል!”  ለማለቱ?

ይልቅስ  እናት-ዓለም  …
”፩ እና ፩”  ብሎ … ሀገር  በዘር  ሲመነዝር
ማዶ  ያሉት  ቀርቦ … መሃሉ  ሳይሆን  ዳር
ዘራፍ!  ለዘራፊ … ይሻላል  ትነቂ
“አኳኩሉ”  ሲባል … “ነግቷልን”  ብታወቂ፤

ቀልድ  ፌዝ  ካልሆነ … ሆድ  ሲያውቅ  ዶሮ  ማታ
የልጆች  ጨዋታ፤
ጨክኖ  መቅበር  ነው … ከፍኖ  ስጋጃ
ዳግም  ላይረገዝ … ተመልሶ  ውርጃ።

1984 ዓ. .

Comments are closed.