
By Admin
ሰሞኑን የኢትዮዽያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን እየታመሰች ያለችበትን ጉዳይ አስመልክቶ ጠቅላይ ሚንስትሩ በሰጡት አስተያየት ላይ ብዙ ተብሏል … እየተባለም ነው። ስለዚህም፦ ተጨማሪ ጩኸት መሆን አንባቢን ማሰልቸት ስለሚሆን፤ ዝም ሳይሉ ዝም እንዳሉ ተቆጥሮ ኣንዳንድ ማህበራዊ ሚዲያዎች “ጠቅላይ ሚንስትሩ ዝምታቸውን ሰበሩ” ሲሉ ባሰራጩት ቪዲዮ ላይ የታዘብኩትን ጥቂት ልበልና ወደ ዋናው የፅሑፌ ርዕስ እመለሳለሁ።
ሲጀመር፦ የዚህን ህገ-ወጥ የጵጵስና ካባ ጥለት በዋነኛነት የጣሉትን ሽምቅ ሽማኔ፥ ከጉድጓዳቸው ወጥተው እንዲህና እንዲያ ስላላሉ “ዝም አሉ” ብሎ ማሰብ ስህተተ ነው። በእርግጥ፦ ከምንሰማው ንግግራቸው ውስጥ ፍሬ መልቀም ቀርቶ ፍርፋሪ መቃረም ያስቸግር ይሆናል እንጂ … ጠቅላይ ሚንስትሩ ዝም ብለው አያውቁም – ወደፊትም አይሉም። ሰውየው ህግ ሲጥሱ የሚያስጥሱት – በህግ አውጫዊ እና አስፈፃሚው አካል አለቃ እንደሆነ ሁሉ፤ ትግራዩንም ሲወግሩ የሚያስወግሩት – ትግራዋይ የሆነ የመከላከያ ኣዛዥ ሾመው፣ ወልቃይትንም ሲነጥቁ የሚያስነጥቁት – ኣማራ ነኝ የሚል ግለሰብ በኮሚቴ ሊቀመንበርነት ሰይመው ነው። ፊት ለፊት ወጥተው “እንዲህ አስደረኩ” ሲሉ ስላልተሰሙ ዝም ያሉ የሚመስለው ከ’አለ … የመሰሪነት ትርጉም ያልገባው ገዋ ብቻ ነው።
የኣንድ ትልቅ social institution ህግና ደንብ ሲጣስ እየተመለከቱ “እኔ አያገባኝም፥ ከእናንተ ውስጥም ቢሆን ማንም እጁን እንዳያስገባ” ሲሉ ካቢኔያቸውን እንደ ህፃን የተቆጡት ጠቅላይ ሚንስትር … ኢትዮዽያን የሚመለከቱዋት ህዝብ በአብላጫ ድምፅ እንደሰጣቸው ትልቅ ኣደራ ሳይሆን፥ ለህዝብ አብላጫ ገንዘብ ከፍለው እንደ ገዟት የጨረታ ዕቃ ነው። መሪ ሆነው ስለተመረጡ፣ ባለው ኣንድ ወንበር ላይ ስለተቀመጡ … የኢትዮዽያና የኢትዽያውያንን ህልውና የሚያስጠብቁበት አመራር በበጎ ፈቃዳቸው ላይ ብቻ የተመሰረተ መብታቸው እንጂ በኃላፊነት የሚያስጠይቅ ግዴታቸው እንደሆነ ገና የተረዱ አልመሰለኝም። በእርግጥ ያለከልካይ፦ ይተክላሉ – ይነቅላሉ፣ ይሾማሉ – ይሽራሉ፣ ያስራሉ – ይፈታሉ፣ ያስገድላሉ – ያጋድላሉ። ኣንዳንዴ የሀገር ጉዳይ ሆኖ ያሳስባል እንጂ፥ ኣንጀቱን ብስጭት እየላጠው መዳፉን በጭብጨባ የሚልጠውን አስመሳይ ማህበረሰብ ስታዘብ … ይበለው! ሲያንሰው ነው! እላለሁ።
ጠቅላይ ሚንስትሩ፦ እንደውትሮው … ከደርግና ህወሃት የተሻልኩ ስለሆንኩ ይህንና ያን አደረኩ … ብለው በደሰኮሩበት መድረክ፥ ለኢትዮዽያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ከህንፃ መመለስ እስከ መሬት “ማውረስ” የተለየ ድጋፍ ማድረጋቸውን ገልፀውልናል። ይህ እንደ ትልቅ ችሮታ ሆኖ የሚቆጠረው ግን ከውጤት በስተጀርባ ለምን? ብሎ ምክንያትን ለማይጠይቅ፣ የሚያየውንና የሚሰማውን ሁሉ ያለመመርመር ለሚቀበል፣ ተቀብሎም በጐ አልያም መጥፎ ድምዳሜ ላይ ለሚደርስ የስንኩል አእምሮ ባለቤት ነው። በእኔ እምነት፦ ሁልጊዜም ቢሆን የውጤት ትክክለኛ ዋጋ የሚተመነው በምክንያት ነው። አቶ አውል አርባ … በክልሌ አፋር ለእስልምና ሀይማኖት ተከታዮች መስኪድ መስሪያ ይውል ዘንድ የሰጠሁት መሬት ለኦርቶዶክስ፣ ካቶሊክና ፕሮቴስታንት እምነት ቤተክርስቲያናት አጠቃላይ ድምር ከሰጠሁት በሦስት እጥፍ ይበልጣል … የሚል ሪፖርት ይዘው ቢመጡ፥ የክልል ፕሬዘደንቱ ለእስልምና ሀይማኖት የተለየ ድጋፍ ለማድረጋቸው ማሳያ ሆኖ የሚቀርብ በቂ ምክንያት አይሆንም።
ያኔ … ወደ ስልጣን በመጡ ኣንድና ሁለት ዓመታት ውስጥ ጠቅላይ ሚንስትሩ ህዝቡን በደንብ ሲያውቁት፥ ህዝቡ ግን ጠቅላይ ሚንስትሩን በፍፁም አያውቃቸውም ነበር ማለት ይቻላል፤ በቁጭ-ይበሉ ፖለቲካ ቁርጭምጭሚቱ እስኪያብጥ ጮቤ አስረግጠውታል። አሁን ላይ ግን፦ ህዝቡ ጠቅላዩን በደንብ እያወቃቸው ሲመጣ፥ እርሳቸው ግን ህዝቡን ወደ አለማውቅ እየተሸጋገሩ ያሉ ይመስለኛል። ለዛም ነው፦ ሁሌ በኣንድና ተመሳሳይ የክራር ቅኝት ሊያስጨፍሩት የሚሞክሩት። ህዝቡ ግን … ገሚሱ ተሰላችቶ ገሚሱም “ነቄ” ብሎ የጠቅላዩን ማይክ እንደ ፊኛ፣ ቃላቸውንም እንደ ባዶ አየር መቁጠር ከጀመረ ከራርሟል። ትላንት በህወሃት መካከል አሜኬላ ለመትከል “ዶ/ር ደብረፅዮንን ስሙት” ሲሉ እንደተደመጡት፥ ዛሬም በኣማራና ትግራዋይ ካህናት መካከል መከፋፈልን ለመዝራት “እንደ ኣቡነ ማትያስ ሁኑ” ሲሉ ጠበል አስመስለው የረጩዋት ጠብ ያለውጤት መክናለች። ይልቅስ … ከቀን ወደ ቀን በየመድረኩ የሚያነሱት ሃሳብ፣ የሚሰጡት ምሳሌና ምላሽ ለኣማራው ብሔር ያላቸውን ጥላቻ ወገግ እያደረገው መጥቷል።
ጠቅላይ ሚንስትሩ ባስሙት ንግግር ላይ ከዚህ በላይ አስፍቼ መሔድ ባልፈልግም፥ በተመለከትኩት የተንቀሳቃሽ ምስል ውስጥ ግን በህይወት መኖራቸውን ጭምር እርስት አድርጌው የነበረውን ጉንቱ የብኣዴን ሰው አይቼ ተገርሜያለሁ። ኣደራ ታዲያ “ምነው ተገረመ? አርፈዋል ብሎ የ YouTube ዜና ለመስራት አስቦ ነበር እንዴ?” ብላችሁ እንዳታሙኝ። ያን ይህልም ጨካኝ ሰው አይደለሁም። ደግሞስ፦ ግድያ ሆኖ “ኣውራው በግ ታረደ!” አልያም በተፈጥሮዋዊ ህልፈት “ሙክቱ በከተ!” የሚል ዜና ምን እርባና አለውና ለYouTube ፍጆታ ይውላል?
ወደ ኢሉአባቦር ልሻገር …
ከዓመታት በፊት “አብቅቶላታል! በኣየር ላይ የተበተነ ዱቄት ሆናለች!” የተባለችው ህወሃት … ተበትና ሳትቀር፥ ተና እና ደምና ኢሉአባቦር ላይ ጎጎ-ቅጫ ሆና አካፍታለች። በእርግጥ፦ “የኢትዮዽያ መንግሥትና ህወሃት የደረሱበትን የሰላም ስምምነት አፈፃፀም ገመገሙ” በተባለበት ስብሰባ ላይ ግራና ቀኝ ተቀመጥው ከተመለከትኳቸው ተሰብሳቢዎችና ካዳመጥኳቸው አስተያየቶች በላይ ግርማ ሞገሱ የመሰጠኝ ዙሪያውን የከበቡት ጠረፔዛ ነው። ለነገሩ ደም መቀባት እና ደም-ግባት ፍፁም የተለያዩ ነገሮች እንደመሆናቸው፥ ደም የተቀባ ሰው ያሳስባል እንጂ ምን ውበት ኖሮት ቀልብ ይስባል?
ገበታ ለሀገር ባሉት ኣዳራሽ መሐል በተዘረጋው ጠረፔዛ ላይ ሲያዩት ገና ጉሮሮን በአምሮት ሀሩር አድርቆ በግድ የሚያስጠማውን የታሸገ ውሃ ስመለከት … ጠቅላይ ሚንስትሩ፦ ወታደሩን አዋግተው ሳይሆን ወግተው፣ ህወሃትን በኪሎሜትር ሳይሆን በከተማ ርቀት ቀድመው አዲስ አበባ ለገቡት የጦር አዛዦቻቸው ሹመት በሰጡበት መድረክ ላይ “ሽንቱን እየጠጣ የተዋጋና የተሰዋ ወታደር አለ” ያሉት ትውስ አለኝ። ለሀገር ክብር ሲባል አባትና ልጅ በኣንድ ቀን ወድቀው … ለወግ ማዕረጉ እንኳ ኣንዲት ዘለላ እንጉዳይ በጉድጓዳቸው ላይ ሳናይ፥ ገዳይና አጋዳዮቹ የተሰበሰቡበት ጠረፔዛ የ’Afri Flora’ን የአበባ እርሻ መስሎ ስመለከት … ከንቱ ሞት ለሞቱት ምስኪን ዜጎች ከኣንጀቴ አዘንኩ። ልብ ላለው ቋሚ ሰብ ግን ይህ ጥልቅ ትምህርት ነው። ከእንግዲህ ቦኃላ የክህደትን ካህን፣ የማስመሰልን መሲህ አምነህ ለጨበጣ ውጊያ ጦርነት አይደለም ለንግስ ጭፈራ ጥምቀትም እንኳ ቢሆን እንዴት አብረህ ትሔዳላህ?
ወታደር፦ ወጥቶ ለማደር ፍቃደኛ ስለሆነ፣ ከህይወቱ በፊት ሀገርና ወገኑን አስቀድሞ ለመጠበቅ ቃልኪዳን ስለገባ፣ መሰዋት እንጂ መሞት አይገባውም። ይህን ስል በመሰዋት (ምክንያታዊ ህልፈት) እና በመሞት (ኃላፊነት በጐደለው ግድያ) መካከል ያለው ልዩነት ግልፅ ነው ብዬ በማሰብ ነው። በፍላጎቱ የውትድርናን ተግባር የመረጠ ግለሰብ ወሩን ጠብቆ የአገልግሎቱን ዋጋ … ደሞዝ … ስለሚቀበል መሪዎችና አዛዦች በንህዝላልነት እንዲያስጨፈጭፉት በቂ ምክንያት ሊሆናቸው አይገባም።
የሲቪሉን ማህበረሰብም ይሁን የሀገር መከላከያ ሀይልን አግባብ ባልሆነ አመራር ህይወቱን ያሳጣ አይደለም … ኃላፊነት በጐደለው ስምሪት ሳቢያ እንኳ በምርኮ ነፃነቱን ያስነጠቀም ቢሆን በህግ ሊጠየቅ ይገባል። ይህ ግን በአሁኗ ኢትዮዽያ ቀልድ ነው። ለጠቅላይ ሚንስትሩም ሆነ ለጦር አመራሮቻቸው ዜጎች እንደ ቼስ ጠጠር መጫወቻዎች ናቸው፤ ለዛም ነው “ጁንታው መለማመጃችን ነው” ሲሉ የዘበቱት። የጦር አዛዦች … ለቁጥር በሚታክት መጠን አማርከው እና አስገድለው በየመድረኩ ሲሸልሉና ሲሸለሙ እንጂ ሲሸማቀቁና ሲጠየቁ አንመለከትም። ይህ እንዲህ የሚቀጥለው ግን ለጥቂት ጊዜ ነው፥ ምክንያቱም የንፁሐን ደም ውሎ አድሮ የሚከፈል የማይሰረዝ እዳ ነውና። ጠቅላይ ሚንስትሩ በ17ኛው የብሄር ብሄረሰቦች እና ህዝቦች ቀን ላይ ባሰሙት ንግግር “እኛ 10 ቦታ ብንበጣጠስ ልጆቻችን ቀጣጥለውና አጉልተው የሚያሳዩት ማንነት አለን” ሲሉ በነሲብ ይሁን በነበይ ኣፍ ያወጡት ቃል … ምንነቱን ወደፊት የምናረጋግጠው ይሆናል።