
By Admin
መንፈሷ … ከውስጧ
ስሜቷ … ከአካሏ
እንደ ጨርቅ ወልቆ
ብቻውን ሲንሳፈፍ … በሙታን ሸለቆ
ገና ሳለች ህያው … ለብሳ እርጥብ ሥጋ
ከሞት መንደር ቆማ … እንደ ሓውልት ተተክላ
ባያት በተመስጦ
ለጋ አጥንቷ ጎብጦ
ምን እንደምታስብ … ማውቅ ቢያዳግተኝ
እንደ ትንሽ ጣቷ … በሃሳብ ብታኝከኝ
ሓጢያት ሊሆንብኝ
ክፉ አምሮት አገኘኝ …
ለኣንዲት ሰከንድ ብቻ
የሌለውን አቻ
‘እግዜርን በሆንኩኝ’
ብዬ ተመኘሁኝ!
እንደ ኤርትራ ባህር … ሀዘኗን ልከፍለው
ውስጧን ያራሳትን … እንባዋን ላደርቀው
ለቅፅበትም ቢሆን
ብችል እሱን መሆን?
ኣጥንት ሥጋ ለብሶ … እርሱ እኔን ከሆነ
እኔም እርሱን መሆን … ቢያስችለኝ ምናለ?
አውሶኝ ጥበቡን
ሰጥቶኝ ተኣምራቱን
እንደ ማርታ ወንድም … ከፊቷ ባቆመው?
ከጉድጎድ አውጥቼ … ውዷን ባራምደው?