
By Admin
ጤና ይስጥልኝ
አብሮ ይስጠን … ምነው ጠፋህ?
እኔን ነው?
ታዲያ ማንን ነው?
አይ መንግስታችንን መስሎኝ ነበር
መንግስታችንማ ሲጠፋም፣ ሲታገስም ምክንያት አለው
የትዕግስቱ ምክንያት እንኳን “ምህዳሩን ለማስፋት ነው” ብለው ጠቅላይ ሚንስትሩ ሲናገሩ የሰማኋቸው መስሎኛል፤ ሰው ሲያልቅ ዝም ያሉበት ምክንያት እንጂ ያልገባኝ
ምድሩን ለማስፋት ነው
እንደዛ በለኛ፥ እስትንፋስ ድምፃቸው ሲጠፋ ተገርሜ ነበር
እሱም ቢሆን አይግረምህ … ሚዲያውን ለማስፋት ነው
ወይ ማስፋት! … ሐዋርያው ጠቅላይ ሚንስትር፦ የአሸባሪዎች መንደርና ምህዳር ሲሰፋ፥ የተሸባሪዎች ሰፈር እየጠበበ፥ ነገ ቤተ–መንግስቱ ደጃፍ እንደሚደርሱ አልተረዱ ይሆን
ደግሞ ዛሬ ሐዋርያ አደረካቸው?
ምን ይጓድላቸዋል? እንደ መጥምቁ ዮሐንስ በውሃ ወይ እንደ መንፈስ–ቅዱስ በእሳት ባያጠምቁንም ደም አልከለከሉንም
እየመረጥክ አታዳምጥ! እንኳን ኋላ–ቀር security apparatus ያላት ኢትዮዽያ ውስጥ ይቅርና አሜሪካን ሀገርም ሰው በሽብርተኞች በገፍ ይረግፋል ሲሉ አልሰማህም?
ሰምቻለሁ። የአሜሪካ መንግስት ባህር፣ ምድር፣ አየር ሀይሉንም ጭምር አዝምቶ ሽብርተኛውን ከዚህኛው የምድር ጫፍ እስከዚያኛው የምድር ጫፍ አስሶ ሲያድን እንጂ፥ በክልሉ ውስጥ ጥበቃ ቀጥሮ እያሳደረ፣ አሽሞንሙኖ እያኖረ … “ምህዳሩን ላሰፋ ነው” ብሎ ሲቀልድ ግን አልሰማሁም … አላየሁም። እሳቸው አይተው፣ ሰምተው ከሆነ ጠይቅልኝ
ወንድሜ እሳቸው ራሺያ እንጂ አሜሪካን አልከረሙም። ደግሞም …
ራሺያስ ቢሆን? መሪዋ ለሽብርተኞች ሽብር እንደሆነ አታውቅም? “TO FORGIVE THE TERRORISTS IS UP TO GOD, BUT TO SEND THEM TO HIM IS UP TO ME” ያለው Putin እንጂ Trump መሰለህ? ነው ወይስ አንተም እንደ አውሮፓውያኑ ለአባባሉ እውቅና መንፈግ ፈለክ?
እና አሁን ምን ይሁን ነው የምትለው? ነፍስ መጥፋት አለበት? ሀይማኖተኞች ነን እኮ
አንተን ብሎ ሐይማኖተኛ! መጀመሪያ በሀላፊነትና በሐይማኖት መካከል ያለው ልዩነት ሊገባህ ይገባል
ገብቶኛል
ቢገባህማ ሰው እንደ በግ በካራ የሚያርድና የሚያሳርድ ወንጀለኛ ቀርቶ፥ “የበግ እረኛ” የነበረውም ክርስቶስም ሁሉ ይድኑ ዘንድ አንዱ ሊጠፋ ግድ ሆኖ በግንድ ላይ ተሰቅሏል
ለስብከት ነው እንዴ የደወልከው?
ስብከቱንማ … መቼም ጠባቂ የሌላቸው አባቶች እየታረዱ ነው … ጠባቂ ላላቸው ጠቅላይ ሚንስትር ትቼዋለሁ። እኔ ግን የደወልኩልህ ተገርሜ ነው
የአንተ ግርምትና የህወሃት መግለጫ መቼም አያልቅም፤ እስቲ ልስማህ
ቀይ–መስቀል የሽንት ባንክ ጀመረ እንዴ? ኣዴፓ “ደም ልሰጥ ዝግጅት ላይ ነኝ” ሲል ሰማሁት
እኔ አልሰማሁም
አተረፍኩሃ!?
ከምኑ
በድንገተኛ አደጋ የኣንዱ ኣዴፓ ደም ተለግሰህ ቁጭ ብሎ ከመሽናት
ሰውዬ … አንተ የኣዴፓ ስጋት አልገባህም መሰለኝ። ከክልሌ ውጪ ከ 15 ሚልዮን ያላነሰ ህዝብ አለኝ እያለ ነው። ይህ ህዝብ ተፈናቅሎብህ ቢጐርፍ ምን ልትል ነው?
እሰየው!
እሰየው?
አዎ እሰየው ነው የምለው! ሲጀመር ታፍኖ ከመሞት ተፈናቅሎ መኖር አይሻልም? ሲቀጥል 15 ሚልዮን ተፈናቅሎ ቢመጣ፥ 15 ሚልዮን ክላሺንኮቭ ይዘህ ትጠብቀዋለህ። ያኔ በነፍስ ወከፍ አስታጥቀህ፦ የትኛው ብሔር … የትኛውን አፈር አብኩቶ …. የትኛውን ማገር ማግሮ ክልል መርጐ “ባለቤት ነኝ!” እንዳለ አብረኸው ሔደህ በምትግባባበት ቋንቋ ትጠያየቃለህ
ጦርነት መፍትሔ አይሆንም ብለዋል ጠቅላይ ሚንስትራችን …
እሰይ የእኔ ኣዴፓ¡ እኔ ምለው … ሰባተኛው ንጉስ ስንት ሉሉ ነው ያላቸው?
ደሞ ማነው ሉሉ?
አንድነት ፓርክ ሔደህ ሉሉ ማን እንደነበረች አፄ ኃይለሥላሴን ጠይቃቸው
እሺ እጠይቃለሁ፤ አሁን ግን ‘ልታሰር’ ነው
ማነው የሚያስርህ?
ኦ ለካ አንተ ሽገርን ተሻግረኃል። መሔዴ ነው ማለት ፈልጌ ነው፤ ከአቶ ጃዋር መሐመድ የኮረጅነው አዲስ ቃል ነው
እንደሱ mood ያዙ
ምን ይለናል! ጥይት ባልጎረሰ መሳሪያ መፎከርና ባዶ እጁን ያለ ጠላትህን ማስፈራራት የምትችለው እኮ ምላጩን እስካልሳብክ ድረስ ብቻ ነው። ኣንድ ጊዜ አእምሮህ ባርቆ፣ ጣትህ ምላጩን ስባ የጨበጥከው መሳሪያ ቀፎ እንደሆነ ከታወቀ … አለቀ! አቶ ጁዋር መሐመድ ‘መላ ቄሮ በመዳፌ ነው‘ ሲሉ እንዳላቅራሩ፥ ዛሬ ተሳስተው ምልጩን ስበው ተፎገሩ
እኔ ግን አልስማማም … የአቶ ጁዋር ኩራት፣ የጠቅላይ ሚንስትሩ ስጋት ‘ቄሮ‘ ሳይሆን ህወሃት ናት። ብረትን የሚስለው ብቻ ሳይሆን የሚያዶለዱመውም ብረት መሆኑን አምነው ጠቅላይ ሚንስትሩ ወጣቱን ለወጣቱ ትተው የአዛውንቶቹን ጉዳይ መላ ቢያበጁለት ይሻላል። አለበለዚያ ግን … አዛውንቶቹን “ባይሎጂው” ሳይቀድማቸው ጠቅላይ ሚንስትሩን ‘ኬሚስትሪው‘ እንዳይቀድማቸው
በል አሁን እንፋታ …
ምነው ቸኮልክ?
ሽምግልና አለብኝ
አንተ?
አዎ እኔ … ምነው? ለሽምግልና አንሳለሁ?
ኧረ በፍፁም! ለሽምግልናም ለሽንገላም አታንስም
አንተ ተሳደብ፤ እኔ ግን ባለትዳር ልሸመግል ነው የምሔደው … ያውም ነፍሰ ጡር ቤት
ነፍሰ ጡሩዋ ሽምግልና አምሯት ነው ወይንስ …
ስድቡ አይበቃኽም?
እውነቴን እኮ ነው። ዘንድሮ ሴቶቹ አያርግዙ እንጂ ሰበብ ነው የሚፈልጉት። በል ቀላሉን ያድርግልህ
ምኑን ነው የሚያቀልልኝ?
አምሮቷን ነዋ! መገንጠል አማረኝ ብላውስ እንደሆን?
ዶ/ር ደብረጽዮን ቤት ነው የምሔደው አልኩህ እንዴ?
የትም ሂድ ብቻ ይቅናህ … ደህና ሰንብት!
አሜን! አብረን ደህና እንሰንብት!