
By Admin
ጤና ይስጥልኝ
አብሮ ይስጠን ሰውየው … ምነው ጠፋህ?
ጠፋሁ አይደል? … በኣንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ ገድላለሁ ብዬ ነበር፤ ግን ባየው ባየው የሚሆን ስላልመሰለኝ፥ ሁለቱም ወፎች ሳይበሩ ብዬ ይኸው ተከሰትኩ
ትንሽ በተን አድርገው እስቲ
ጠቅላይ ሚንስትሩ እንደ አርተፊሻሉ ዝናብ ሹመት ሲያዘንቡ ተምልክቼ፥ ለፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ የዘነበ ለአንተም ያካፋል ብዬ ጠብቄ ነበር። ያው ዘግየት ብዬ ደውዬ “እንደምን ሰንብተሃል?” ብቻ ሳይሆን “እንኳን ደስ አለህ!” ጭምር ለማለት
ቂል ነህ ልበል?
በል … ግን እኔም “እንዴት?” ልበል?
ወታደር እኮ የሚኖረውም የሚሞተውም ለህዝብ እንጂ ለኣንድ መሪ አይደለም። ስለዚህ የወታደርን የአገልግሎት ዋጋ መተመንም ሆነ መክፈል ያለበት የህዝብ ህሊና ነው። ህዝብ ሥራህን መዝኖ – “ይገባዋል!” ብሎ ካልፈረደ፥ ማንም ተነስቶ “ጥቁር ኣንበሳ” “ነጭ ዝሆን” እያለ ደረት – ትከሻህን በቁራጭ ጨርቅ ቢያስጌጠው፥ ተገልብጦ ከውጭ የተሰፋ ተራ የልብስ tag ከመሆን ባለፈ ምን ጥቅም አለውና ነው … ብሸለም … “እንኳ ደስ አለህ!” ልትለኝ የምታስበው? ህዝብ ያልተቀበለው የወታደር ሹመት … ልክ እንደ ነጠላ ጥለት ልብስ ማድመቂያ እንጂ ጅብዱ መግለጫ – ሞራል ማሞቂያ እንደማይሆን አታውቅም?
በል በል ፊልድ ማርሻሉ ሰምተው ሸዋ ሮቢት field እንዳትወጣ
ሸዋ ሮቢት … ቂሊንጦ … የፈለጉት ቦታ ቢወስዱኝ እውነቱ ይኸው ነው። ህዝብ አምኖ ካልሰጠህ፥ መሪ እንድታምነው የሚሰጥህ የወታደር ማዕረግ እንደ ብጫቂ garment label የልብሱን ስሪት እንጂ የለባሹን ሥራ የማሳየት ጉልበት የለውም። ያልተገባ የወታደር ማዕረግ ውበቱ ለልብሱ እንጂ ለለባሹ ከንቱ ሸክም ነው፤ ምክንያቱም ሹመት ስልጣን እንጂ ዕውቀት አይደለምና
ምን ኣይነት የክት ትርክት ይዘህብን መጣህ ደግሞ?
ይኼ የክት ትርክት ሳይሆን የአዘቦት ዕውነት ነው። ኣንድ ባለስልጣን ካልተመቸህ ሹመቱን ነጥቀህ ተራ ሠራተኛ ልታደርገው ትችላለህ፤ ልክ ኣንድን ጄነራል ማዕረጉን ገፈህ ተራ ወታደር ልታደርገው እንደምትችል ማለት ነው። ኣንድን ምሁር ግን ቢመችህም ባይመችህም ዕውቀቱን ነጥቀህ ልታደድበው አትችልም
ቆይ … ወታደሮቹ ሹመት አይገባቸውም ነበር ነው የምትለኝ?
አልወጣኝም
እና ታዲያ?
ሹመቱ መሰጠት የነበረበት ለተራ ወታደሩ፦ የመድፉን ጩኸት፣ የክላሹን ፉጨት በቅርብ ሜዳው ላይ ለሰማው እንጂ በ40 እና 50 ኪሜ ርቀት ላይ ሆኖ “ሽሽ!” እያለ ሲሸሽ አምሽቶ ኣዲስ አበባ ለገባው መሆን አልነበረበትም ነው የምልህ
አሁን ገባኝ፤ አዛዦቹ ዕድገት አይገባቸውም ባይ ነህ
አዎ! እነሱን ከፈለጉ ጠቅላይ ሚንስትሩ በዕድገትም ይሁን በክህደት ወደ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ያዛውሯቸው። ሯጮቹን ያሰልጥኑ። ለነገሩ እሳቸውም ቢዛወሩ ጥሩ ነበር። ወራሪን በአስወራሪ እንዴት ትዋጋዋለህ?
በቃ ተግባብተናል፤ ሀሳቤን አንስቻለሁ
Good. ጥሩ ጓደኛዬ ከሆንክ፦ ከጠቅላይ ሚንስትሩ የትከሻ ማዕረግ ሳይሆን ከኣንዱ በጎ አሳቢ ተራ ክራቫት እንድሸለም ተመኝልኝ
ኧረ በሚገባ! ግዛልኝ አትበለኝ እንጂ ለምኞት ለምኞትማ ክራቫት አይደለም ሙሉ ሱፍ ነው የምመኝልህ
እየቀለድክ ነው?
ለምን እቀልዳለሁ?
ታዲያ እንዴት ነው ሱፍ መብላት በከበደበት ሀገር ሱፍ መልበስ የምትመኝልኝ? ማን ተርፎት ነው የሚያለብሰኝ?
በጣም ይቅርታ! ከኣንድ ሚልዮን በላይ ዲያስፖራ ገብቷል ስትሉ ኢኮኖሚው ትንሽ ነፍስ ዘርቷል ብዬ በማሰብ ነው እንጂ ለቀልድ አልነበረም
እዋይ! አለ ተክላይ። ዲያስፖራው ኢኮኖሚው ላይ ነፍስ ሊዘራ አይደለም ለእራሱም ነፍስ–ግቢ ነፍስ–ውጪ ላይ ነው
ምነው ? ኮሮና ነው?
ኮሮናማ ቢሆን ታሞ በዳነ፤ ጠቅላይ ሚንስትሩ “ና ግባ” ብለው … እንደ ገና ኳስ በዋዜማው በዱላ አንክተው አንክተው ዘረሩት እንጂ
lol … እስረኞቹን ፈተው ነው?
እስረኛማ ጊዜውን ጠብቆ ይፈታል፤ ደንብ ነው። ገዳዮቹን ለቀው በል እንጂ
እንደዚህ ነው አየህ፦ በትንቢት መንገስ ትዕቢተኛ ያደርጋል፤ ህዝብን ያስንቃል። ኣንድ መሪ ከእግዚአብሔር የተላኩ ነኝ ብሎ ሲያስብ አገዛዙ ፍፁም መስሎ ስለሚሰማው በዙሪያው ላለ ድምፅ ጆሮውን ይዘጋል። እርሱ የነካው ሙጃ … አገዳ፣ ቅጠሉ … ጐመን የሚሆን ስለሚመስለው የሰውን ስሜትና ፍላጎት ለማወቅ አይፈቅድም። አሁንም የሆነው ይህ ነው። ይብላኝ እንጂ ለእርሳቸው … .
ለእኛ በል እንጂ ፤ ከዛሬ ነገ ይሻላል ብለን ስናስብ ጉድ ለተሰራነው። ለምጣዱ ሲባል አይጧ ትለፍ ብለን ዝም ብንል ጭራሽ ጭራውን አቁሞ አይጠ–ሞገጡ መጣ ። ደግሞ “ለሀገር ሰላምና ዕድገት ሲባል የተወሰደ እርምጃ ነው” ይባልልኛል። ለሀገር ሰላምና ዕድገት ከታሰበ’ኮ መሪው መጠየቅ ያለበት “ባላገሩ ምን ይላል?” ብሎ እንጂ “ባይደን ምን ይፈልጋል?” ብሎ አልነበረም
ለዛ እኮ ነው … ይብላኝ ለእርሳቸው ያልኩህ። ሀገርህን አርክሰህ ባዕዱን በማዋደድ መንግስትህን የምታፀና ከመሰለህ የዋህ ነህ። የኣንድ አገዛዝ መውደቅ ወይንም መቆም ዕድል ፈንታ የሚወሰነው በምዕራቡ ዓለም ጫጫታ ሳይሆን በህዝቡ ፍቅርና አመኔታ እንደሆነ አሜሪካ ጥግ ሄደን ኩባን፣ አፍሪካ ጫፍ ተጉዘን ዝምባብዌን መመልከት አያስፈልገንም፥ እዚሁ አፍንጫችን ስር ያለቸው ኤርትራ ምስክር ናት። እነርሱም ብልጦች ናቸው ይህን ስለሚያውቁ፥ ሊያጠቁህ ሲፈልጉ መጀመሪያ ከህዝብህ ይነጥሉሀል። እባብ የሆነውን የምዕራቡን ዓለም ያስደሰተውም የእስረኞቹ መፈታት ሳይሆን የጠቅላይ ሚንስትሩ ከብዙ ደጋፊያቸው መፋታት ነው
ያም ቢሆን ለምን “ይብላኝ ለእርሳቸው” ብዬ እኔ እበላለሁ? ሲፈልጉ እራሳቸው ይበሉ እንጂ
ሎል … ማን ይበላቸዋል ብለህ ነው? ህወሃት?
ምናልባት
አትሳሳት! በዘር ደም ስር ለተወሰወሰ ዘረኛ ፍጡር ሺ ጊዜ ብትጣፍጥ ማስቲካ እንጂ ማር አትሆንም፤ አኝኮ ይተፋሃል እንጂ አላምጦ አይውጥህም። ጠቅላይ ሚንስትሩ ዝም ብለው ነው የደከሙት። ቅኔው ከገባህ 🙂
ቅኔውንማ “ህወሃትን በገንዘብ ቀየርነው” ብለው በ 21ኛው ክፍለ ዘመን ወደ “ባሪያ ንግድ” ላሸጋገሩን የመንግስት ደላሎች (ፈንጋዮች) ትተነዋል
ምነው? በእስረኞቹ ሽያጭ በቅርቡ ይገዛል የተባለው “ትልቅ” የሀገር ብልፅግና አልተዋጠልህም?
“ብልፅግና” ነው ያልከው?
አዎ፤ ብልፅግና … ኣዲስ ምዕራፍ … ማማ …ከፍታ … Pan African-ism … ስንቱን ልዘርዝርልህ
ማን ነበር “የምትበላው የላት … የምትከናነበው አማራት” ያለው?
ያ ተረትማ ዱሮ ቀረ። አሁን “የምትበላው የላት … የተከናነበችውን መሳደብ አማራት” ሆኗል የሚባለው
ማለት?
ባዶ ሆዳን እየተንከባለለች “ፎጣ ለባሽ” ብላ የምትጮህ አላጋጠመችህም?
lol በል ደህና ሰንብት። መጠፋፋት ያረሳሳል … አስብበት
እሺ አልጠፋም። መልካም ሰንብት