
By Admin
ከጥቂት ቀናት በፊት “ወጣቶች እየመጡ ነው፤ ወጣት፥ የነብር ጣት፤ ግንቦት ፯ በወጣቶች የተገነባ ድርጅት … ” የሚል መጣጥፍ አነበብኩ። እርግጥ ነው የዚህ ትኩስ ሀይል ለውጥ ፈላጊነትና የለውጥ አስፈፃሚነት ሚና አያከራክርም። ጹሁፉ በጅምላ የኢትዮዽያን ወጣቶች የዳሰሰ፡ እኔም ሙሉ በሙሉ የምጋራው አስተውሎት ቢሆንም፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከታዘብኩት እውነታ ተነሰቼ፣ ወጣቶቹንም በችርቻሮ ከፋፍዪ፡ ለምን “መጡ” ከተባሉት የግንቦት-7 ወጣቶች ጋር በምሳሌና ተረት ትንሽ እንጫዋወትም ብዪ ፊደላትን መደርደር ጀመርኩ።
ገሚሱ ዲያስፖራ፦ ሻቢያ፣ ግንቦት-7 እና ኢሳት በአካል እንጂ ሶስትነታቸው፡ በመንፈስና በግብር እንደ ስላሴ ኣንድ ናቸው፤ በሚል የፖለቲካ ስነመለኮት መጓተት ከጀመረ ትንሽ ሰነባበተ። የግንቦት-7 ከሻቢያ ሁለንተናዊ ድጋፍ ማግኘትም ሆነ በሶስቱ አካላት (በሻቢያ፣ በግንቦት-7 እና በኢሳት) መካከል ያለው ጠንካራ ሠንሰለታዊ ትስስር ፀሀይ የሞቀው የአደባባይ ሃቅ ሆኖ ሳለ ዛሬ ለምን እንደ አዲስ ተከለሰ፣ ተኮነነ አንልም። የንስር ዓይናችን ተቃውሞው የተወሰወሰበትን ግላዊም ሆነ ድርጅታዊ ስውር ክር ነጥሎ ለመመልከት አይሳነውምና። ይህን ሚስጢር እዚሁ ላይ አስረን፡ ወደ ጽሁፉ መንፈስ ስንመለስ፦ ፕሮፌት (ነብዩ) ኢሳያስ “ኢትዮዽያ እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች” አለ እንጂ፤ እግዚአብሔር “ኢትዮዽያ እጆችዋን ወደ ፕሬዝዳንት ኢሳያስ ትዘረጋለች” አላለምና፡ መቼም ቢሆን ዜጎች – ከሻቢያ ጋር ህብረት ለምን? ብለው ሲጠይቁ እንደ መናፍቅ – ይሁዳ ተቆጥረው መወገዝ የለባቸውም።
ትላንት ግንቦት 1 ልደታ ደጃፍ የኔታ ሲያሰተምሩ፦ “ምዕመን ሆይ ለሁሉ ሀጢያታችሁ ንሰሃ ብትገቡ ስርየትን ታገኛላችሁ፤ ይቅርታ የሌለው መተላለፍ ግን መንፈስ-ቅዱስን መስደብ ነው” ነበር ያሉን። ዛሬ ውለን አድረን፡ ቀኑ ገስግሶ ባታን እና አቦን አልፈን ግንቦት ሰባት ብለን ቆጥረን ስላሴ ላይ ስንደርስ፡ ስነ መለኮቱ ተቀልብሶ፣ መንፈስ-ቅዱስ በ መገናኛ-ብዙሃን ተተክቶ፣ ኢሳትን የተናገረ፣ የተቸ አይማረኝ ብምረው፤ በሰባት እጥፍ እሳት ባለበልበው፤ የሚል ፖለቲካዊ መርገምት “መጡ” ከተባሉት ወጣቶች ሲወርድ እየሰማን ነው።
ግንቦት-7 “ኣራተኛ ዙር አሰልጥኜ አስመረኩ“፣ “ገነቡኝ” የሚለን ወጣቶች እነዚህ ሰማያዊ፣ አረንጎዴና ሃምራዊ ሬንጀር መለዮ (ኒክ) ተላብሰው ከዌብ ዌብ እንደሸረሪት እየተወረወሩ በጸያፍ ነውረኛ ስድብ የሰው አናት እና እናት ላይ ዱብ የሚሉተን ፓራኮማሪቶች ከሆነ ነገር ብቻ ሳይሆን ሀገርም ተበላሸ የሚያስብል ነው።
እርግጥ ነው online ሶሻል ሚዲያ የአደባባይ መድረክ ሆኖ ማን ማንን ወክሎ ምን ተናገረ የሚለውን በትክክል ለመፍረድ አያስችልም። ሆኖም ግን ዋልጌ ዌብ-አደሮች (የወያኔ ካድሬዎችንም ጨምሮ) ያሻቸውን “ማልያ” አጥልቀው እንዲጫወቱ፣ አመቺ መስሎ በታያቸውም በር ያለምንም ተከላካይ ጎል እንዲያስቆጥሩ ሜዳውን ከፍቶ የሰጣቸው ግንቦት-7 ለመሆኑ ጥርጥር የለውም። የአመራርሮቹ ዝምታ፦ ሁሉንም ደጋፊ፣ ተወካይ፣ ሲያስፈልገውም ቃል-አቀባይ መስሎ እና ሆኖ ያሻውን አንዲናገር፣ እንዲፅፍ ከፍተት ፈጥሮለታልና።
ሲሆን ሲሆን እንደ ህዝበ-እስራኤል፡ በኤርትራ በር –በቀይ ባህር ልንሻገር ራዕይ አለን የሚሉት መሪዎች በተገኘው የሚዲያ አጋጣሚ ሁሉ ተጠቅመው የጥያቄውንም ሆነ የጥርጣሬውን ደመና መበተን ሲገባቸው፡ በንቀት እና በቸልተኝነት ዝምታን በመምረጣቸው፡ የተቋጠረው ደመና እዚህ ሲሉት እዚያ እየዘነበ ይኸው ዛሬ ያልታሰበ ደራሽ ከራስ አልፎ የቤተሰብን ስም እና ክብር ሲንድ እያየን ነው፤ ነገ ደግሞ ንብረትና ህይወት ይቀጥላል።
እዚህ ላይ ሁላችንም ልናሰምርባት የሚገባው ቁም ነገር ቢኖር፡ ግንቦት-7’ትን ጨምሮ የየትኛውም ተቃዋሚ ድርጅት አመራር አባላት ግዙፍ ሰዉነታቸውን ከቦታ ቦታ፣ ከሀገር ሀገር የሚያንከባልሉትና ዝግ አንደበታቸውን የሚከፈቱት፡ እንደ ሰፈር እቁብ በየሳምንቱ በሚጠራው የገቢ ማሰባሰቢያ (fund raising) የሚጠራቀመውን ብር ብቻ ሳይሆን እንደዚህ እንደ አሁኑ በረባ ባልረባው የፖለቲካ ሽኩቻ ተደናብሮ የሚበታተነውንም መንጋ ለመሰብሰብ ጭምር መሆን እንዳለበት ነው።
መሪ የመሆን ህልም ያላቸው ግለስቦች፡ ሊመሩት የሚናፍቁትን ህዝብ “ይህ ተምሯል ይመጥነኛል” ፣ “ያ ፊደል አልቆጠረም ያንስብኛል” እያሉ ለውይይት የሚሄዱበትን ማህበረሰብ በዕውቀት እና በሃብት የሚከፋፈሉ ከሆነ ትልቅ ስህተት ነው። ሀብታሙም ደሃው፣ ሴቷም ውንዱ፣ የተማረውም ያልተማረው፣ ወጣቱም ሽማግሌው፣ ዓይናማውም ዕውሩ … ሁሉም የሚጥለው የምርጫ ካርድ፡ ገበያ (ቆጠራ) ላይ ዋጋው ኣንድ እና እኩል ነው። የዛሬን አያድርገውና፡ ድሮ ድሮ ህብረተሰብን ለማስተዳደር አዋጅ ሲረቅም ሆነ ሲፀድቅ ከምሁሩ በፊት “እረኛው ምን አለ (ምን ይላል)” ነበር ቀዳሚ ጥያቄው። ዴዚዴራታም ቢሆን “ሆን ብሎ ለሚያዳመጣቸው፡ ከጯሂዎች እና ከደደቦችም ቁም ነገር አየታጣምና ጆሮህን አታቦዝን ” ይላል። የኖህ መርከብ ስትገነባ በተራ አናጢዎች (amateaur joiners)፡ ታይታኒክ ደግሞ በአዋቂ መሃንዲሶች (professional engineers) ቢሆንም፡ ታላቁን የተፈጥሮ ሀይል ተቋቁሞ ህይወትን ማትረፍ የተቻለው በየትኛዋ መርከብና በማን እጅ ሥራ እንደሆነ ልብ ማለቱ፡ ንቀት የድንቁርና አልያም የትዕቢት ምልክት መሆኑን ያስተምራል።
ከሀቅ ላለመራቅ፡ ለእኔ እና እንደ እኔ፡ በር እስከተገኘ ድረስ የሰቆቃችንን አውራ ለማደን፡ ይህም ባይሳካ እንኳ ሃሳብ እና አትኩሮቱን ለመበታተን፡ ግንቦት-7 በኤርትራም ሾለከ በካራማራ፡ የኮሽታ ድምፅ ምንጩን ማብዛቱ ጥቅም አንጂ ጉዳት የለውም። ከዚህም ባሻገር፡ የወያኔን ጠንካራ እና የተነቃነቀ ጥርስ ለይቶ ለማወቅ፣ አውቆም ለመንቀል ከሻቢያ በላይ ጠቋሚ አካል ይኖራል ብዪ አልገምትም። ኣንድ ጡት ባይጣቡም ኣንድ ጡት ነክሰዋልና። ይህ ሲባል ግን መሰረታዊ የሀገርና የህዝብ ጥቅም ለዕርዳታ ከድርድር ውስጥ የሚገባ አየደለም። በቅሎን ከምድረ ገፅ እናጠፋለን ብለን፡ ፈረስ እና አህያን በኣንድ ጋጣ እያረባን በቅሎን ስናድን ዕድሜያችንን መፍጀት ይሆናል።
አንድ አንዴም ኳስ በመሬት አድርገን፡ ትንሽ አየር ስበን፦ “የአንጀት ወዳጅ መስሎ … ትልቅ ጉድጓድ ምሶ፣ ንጉስም ለብልሃት … ያበላል ደግሶ” የሚለውን ዜማ ማዳመጡ አዝናኝም አስተማሪም ነው።
የኧብ ሻቢያ ድጋፍ ለምንና እስከ የት ድረስ ነው? ሻቢያ፦ ኢትዮዽያ በቀል ተቃዋሚዎችን የሚያደራጀው እውን ወያኔን ለመጣል ነው ወይንስ ምናልባት ሀገር ወስጥ የሚዋዥቀው ማዕበል ሻቢያ-ሸብ የሆነውን መንግስት ባልታሰበ ወጀብ ቢነቅለው፡ በምትኩም ሃገራዊ ስሜት ያለው ፀረ-ሻቢያ ዘር በድንገት ቢበቅል “የሃገሩን ሰርዶ በሃገሩ በሬ” ለማስወቃት? ይህስ ባይሆን የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር – ለኢትዮዽያውያኑ ባዕድ ነው፣ አይራራም – ብለው ራሳቸውን በሻቢያ እሾህ አጥረው፡ ለነፍስም ባይሆን ለስጋዊ ደህንነታቸው አስተማማኝ ዋስትና እንደነበራቸው ሁሉ፡ አቶ ኢሳያስም የኢትዮዽያን ተቃዋሚዎች ለኤርትራ-በቀል አፈንጋጮች ማፈኛ ሊያደርጉት? ይህን እና ይሄን የመሳሰሉ ሉዓላዊ ጥያቄዎች፣ ህዝባዊ ስጋቶች ሲከሰቱ፡ ተናገሮ ከማሳመን፣ ጽፎ ከማሰረዳት ይልቅ “ጆሮ ዳባ ልበስ” ማለቱ፡ “የአባትህ ቤት ሲዘረፍ አብረህ ዝረፍ” ከሆነ፡ ከወያኔና ከሻቢያ ተርፎ የሚዘረፍ ዘረኝነት እንጂ ኣንድም ንብረት የለምና ከንቱ ዝምታ ነው።
ሚዛናዊ ትችት ተገቢ ነው፤ ያነፃል፣ ያንፃል። እውነተኛ ነቀፋ ኢሳትን ዓይንና ጆሮ ከመሆን ባሻገር፡ የኢትዮዽያ ህዝብ ምላስ (አንደበትም) ያደርገዋልና መ’ዋጥ እንጂ መተፋት አይኖርበትም ባይ ነኝ። የማሳይህን ብቻ ተመልከት፣ የምነግርህን ብቻ አዳምጥ ከማለት በተጨማሪ “ምን ትላለህ? ተናገር?” ብሎ መድረክን ማመቻችት፡ ህዝባዊ ነኝ ለሚል ሚዲያ ኣንዱ መመሪያ ሊሆን ይገባል። ኢሳት “አሁን ነድጃለሁ፣ ተቀጣጥያለሁ፤ ከዚህ ቦሃላ ቆስቋሽ እና አንዳጅ ትንፋሽ አያስፈልገኝም ” የሚል ከሆነ እንኳን “ልጅ ነው፣ ገና ኣራት ዓመቱ” የሚባል ብልጭታ አይደለም፡ ሀገር የሚለበልብ ሰደድም በራሱ ጊዜና ሰዓት ነዶ መክሰሉ አይቀርም።
ገንቢና መልካም የሆነን አስተያየት በደፈናው እንደነቀፋ እይቆጠሩ፡ ንጹሀንን በመደዳ “ወያኔ – ባንዳ” እያሉ በመፈረጅ የአንባቢን አይን፣ የአድማጭን ጆሮ ክብረ ንፅህና በፀያፍ ስደብ በአደባባይ መግሰሱ ጅልነት ሆኖ ያሳፍራል እንጂ ጀግንነት ሆኖ አያስከብርም። ሀገርና ህዝብን የሚያናጋ ስልጣን ለመጨበጥ እየተንደረደሩ፡ ካልደገፍከኝ አትቃወመኝ፣ አትናገር – አትንካኝ፣ አርፈህ ተቀመጥ – አታቁመኝ፣ ማለት አይቻልም። ትላንት፦ አያት ቅድመ-አያቶቻችን “ሳይቃጠል ፥ በቅጠል” እንዳሉት፤ እኛም ዛሬ፦ ትዕቢቱ፣ ንቀቱና ዛቻው ስጋት ከሆነን፦ ሳይገድልህ በጥይት ፥ በቃላት ብለን መፃፍ እና መጮሃችን አይቀሬ ነው። ዛሬ ወያኔ “የእኔ” ብሎ መዝግቦ ካርድ ካደላቸው ይልቅ፡ የተቃዋሚው ጎራ በግድ ገፍቶ፡ ከራሱ ገምሶ ያዋሰው አባላቶቹ ቁጥር ይበልጣል። ሙሽሪትም ትሁን ጀሚላ፡ ሰጥአርጌ ሆነ ቶላ፡ የግንቦት-7’ትን አቋም፣ የኢሳትን አካሄድ የጠየቀ ማንኛውም ዜጋ፡ ተገፈቶም ቢሆን ተገፍትሮ ከወያኔ ጎራ ይውድቃል። ለግንቦት-7 ደጋፊዎች፣ ለኢሳት አፍቃሪዎች “ለምን?” እና “እንዴት?” ብሎ መጠየቅ “መወየን” እና “ወያኔነት” ነው። ይህ አይነቱ ጭፍን አመለካከት ደግሞ ሀገርን ከባርነት አይደለም ራስንም ከመሀይምነት አያላቅቅም።
እዚህ ላይ፡ ለትግልም ይሁን ለስድብ “መጡ” የተባሉት ወጣቶች፡ አቅማችንም ሆነ አቋማችን ተቃዋሚው ሰለገፋን ወይንም ደግሞ ደጋፊው ሰለሳበን በየማለዳው የሚቀየር፡ በስደት ለስደት ተወልዶ በስለት የቆመ እንዳልሆነ ሊያወቁት ይገባል። የተሰማንን፣ የታየንን፣ ለሀገር ለወገናችን ይጠቅማል ብለን ያሰብነወን ከመናገርና ከመጻፍ የሚያቆመን መብራትም ሆነ ፍርሃት አይኖርም። ይህ ትውልድ ሀቅ እንጂ ሀይል አይገዛውም። ትክክለኛውን የአማርኛ ፍቺ ባላገኝለትም የፖለቲካ ዕምነታችን ፓሽን (passion) እንጂ ፋሽን (fashion) አይደለም። ስንቃወም ባህላዊ ሆነን በልምድ እና በአዘቦት ጎራችንን እንዳለየን ሁሉ፡ ለመደገፍም ዘመናዊ ሆነን በጥራዝ ነጠቅ ቋንቋ “ምን ይለናል” ብለን የአቋም ለወጥ አናደርግም። ለሁለት መስመር የፖለቲካ ድርጅት የድጋፍ ደብዳቤ ሲባል፡ ሁለት ኣስርት ዓመታትን ለሀገር ነጻነት እየታገለ ያለን ዜጋ፡ ኢትዮዽያዊነት ብቻ ሳይሆን ሰብዓዊነት በጎደለው ፀያፍ ቃላት ማቃለሉ፡ ራስን ብቻ ሳይሆን እደግፈዋለሁ የሚሉትንም የፖለቲካ ድርጅት ገብረገባዊ ዲሲፒልን ጥያቄ ውስጥ የሚከት ነውና ብንተራረም መልካም ነው።
እርስ በርስ መጠላለፉም ሆነ መዛለፉ ለማናችንም አይጠቅምም። በአነስተኛና እና ጥቃቅን አስተሳሰብ ተደራጀተን፡ ግላዊና ድርጀታዊ ሆነን፡ እንደ ቅማንት እንደ እንድብር ሳይሆን፡ በኣንድ ላይ ተሰባስበን እንደ ኢትዮዽያዊ ለኢትዮዽያ ማሰብ ብንጀምር ጠቀሜታው ሀገር አቀፋዊ ይሆናል። ዛሬ መደማመጥ ካልቻልን ነገ መደማማታችን አይቀሬ ነው። የእኛን ችግር እኛው ከመፍታት ውጪ ሌላ ምርጫ የለንምና ገመድ ጉተታው ይብቃ። አንገትና ዓይናችንን ወደ አውሮፓና አሜሪካን አንጋጠን፡ እንደ ሰባ ሰገል በዳዊት ኮከብ ምሪት ከሰላም አለቃው በረት ደጃፍ ለመድረስ ማሰብ፡ እጅግ የቆየ ኦሪታዊ ምሪት፣ አድካሚ ጉዞ ነው። ለዚህም የቅርቡን እውነታ፡ የጆን ኬሪን ጉብኝት እንደምሳሌ ብንጠቅስ እንኳ፡ የዘይት እና የዓባይ ተፋሰስ እንጂ የንፁህን ዜጐቻችን ደም መፍሰስ ጣኦቶቻችንን እንዳላሳሰባቸው የተጓዘበት ሃገራትና ክልል ማስረጃ ነው።
ዘንድሮ፡ ምንም እንኳን ወጣቱ ዘካሪ እንጂ መካሪ አያስፈልገኝም ቢልም፡ ጽሁፌን ከማጠቃለሌ በፊት፡ አሁንም በድጋሚ እናንተ ወጣቶች– የፋይበር ኦፕቲክስ በራሪዎች –የኢሳት፣ የግንቦት-7 እና የነብር ጣቶች፡ እባካችሁ ከእኛ በላይ ደጋፊ – concrete ፣ ከእኛ በላይ አጥቂ – MIG Jet ማለቱን ትታችሁ፦ አደብ ግዙ፤ ዕብደት ቀነሱ። በባህላዊ አልባሳት ብቻ ሳይሆን ሀገራዊ በሆነ ባህርያዊ ጥለትም ተጠበቡ፤ ጨዋና ገብረገባዊ ሁኑ እላለሁ።