
By Admin
ጠቅላይ ሚንስትሩ “የኣንድ መቶ ቀን የሥራ ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ” በሚል መሪ ሐሳብ ከሚንስትሮቻቸው ጋር ባደረጉት ስብሰባ ላይ የትግራይ ተወላጆችን እሥር አስመልክቶ ተቆጭተው ሲናገሩ ብቻ ሳይሆን፥ ከዚህም የተነሳ፦ አዳሜ … “It’s My Dam” እያለ ከደረቱ እስከ facebook ድህረ–ገፁ ለጥፎ “ያዙኝ ልቀቁኝ” ሲልለት የነበረውን የህዳሴ ግድብ ወኔ ሳይቀር ከኣባይ በላይ ውሃ ደፍተውበት … “ሳይገነባ ይቅር” ተብሎ ሊተረጎም በሚችል አገላለፅ ሲያራክሱት አዳመጥኩ፤ ግን አልተገረምኩም። ምናልባት፦ “ለምን?” ብላችሁ ከጠየቃችሁኝ ደግሞ … ለጉልበተኛ ብቻ የሚርዱ፣ ጉልበት የለውም ብለው ያሰቡትን ደሀ አደግና ምስኪን ግን አብዝተው የሚንቁ ሰው መሆናቸው አስቀድሜ ስለማውቅ ነው።
ድፍን ሶስት ዓመት ሙሉ፦ የኣማራይቷ ፅንስ በካራ ጨንግፎ ሲፈስ … ቃል ያልተነፈሱ፣ ህፃናት ሴቶች አሮጊቶችና ዓየነ–ስውራን ሳይቀሩ ለመናገር በሚዘገንን ጭካኔ የገጀራና የቀስት ሰለባ ሲሆኑ … ዝምታ የመረጡ፣ ዕድሜ ጉልበት – በሽታ ደግሞ አቅም ነስቷቸው የሰባና የሰማንያ ዓመት አረጋውያን ከደዌ አልጋቸው ላይ እየተጎተቱ በካራ ሲታረዱ … “ጆሮ ዳባ ልበስ” ብለው ያስቸገሩን ንጉስ፥ ይኸው ዛሬ “የትግራይ ተወላጆች ያለአግባብ ታሰሩ” ብለው ሚንስትሮቻቸው ላይ ሲጮኹ ለመስማት በቃን። ታዲያ፦ የኣማራውን ሞትና ህይወት ከቁብ ባይቆጥሩልንም እንኳ … ቢያንስ ግፍን የሚያይ ዓይን፣ በደልን የሚናገር ኣፍ እንዳላቸው በማወቃችን ብቻ “ተመስገን!” አትሉም? “አጃኢብ ነው!” ይላል ሐረሬው … እንደ እኔ ነገር ግርም ሲለው።
እንደ እውነቱ ከሆነ፦ ጠቅላይ ሚንስትሩ ከኣማራው ግድያና ሞት የበለጠ የትግራዋይ እስራት ያሳስባቸዋል፣ ያንገበግባቸዋል ብዬ በፅኑ ባምንም፥ ይህንን በኣደባባይ ለመናገራቸው ምክንያት ግን የተመለከቱት የፍትህ መጓደል ሳይሆን ውስጣቸውን ሞልቶ የሚፈሰው “ልወደድ” ባይነታቸው ነው። እኔም ሆንኩኝ የትኛውም ሰብዓዊ ኢትዮጵያዊ፦ ኢፍትሐዊ እስርም ሆነ ግድያ በአረጋውያን ላይም ሆነ በወጣት ዜጎቻችን ላይ ይፈፀም የሚል አስተሳሰብ የለንም። ነገር ግን፦ የሰው ልጅ ቆዳው እንደሚገፈፍ በግ ተዘቅዝቆ ሲሰቀል ኣንዲት ቃል ለመናገር አንደበታቸው የደረቀው ግለሰብ፥ ዛሬ ይህንን ያህል አምርረው ሲናገሩ መስማት … እራሳቸውን አፅድቆና አዋዶ ሌላውን የመኮነንና የማራከስ ተለምዷዊ ባህሪያቸው መገለጫ ከመሆኑም ባሻገር፤ ማንን ከምን የተነሳ እንደሚፈሩ፣ ማንንስ ስለምን እንደሚንቁ በግልፅ የተነፈሱት ሐቅ ነው።
የንጉስ ኣፍ መሆን እውነታን አጣሞ ህዝብን ለመካድ እንጂ ኬክ ለመቅመስ አይጠቅምም
ኣማራ፦ መረረህም ጣፈጠህም ይህን እውነት መዋጥ አለብህ። የሃምሳ ብር ካኔቴራህ ላይ “ከመከላከያ ጎን እቆማለሁ” እያልክ የምታቅራራው አንተ እንጂ፥ መከላከያው ከአንተ ጎን አልቆመም። ያ ባይሆን ኑሮማ ለኣቅመ–ሔዋን ያልደረሰች የወሎና ሸዋ ልጃገረድ ልጅህ በራስህ ቤት – በራስህ ደጃፍ ላይ ወላጅ እናቷ እየተመለከተች ባልተደፈረች፣ ጎበዛዝቶችህም ጥይትና የቡድን መሳሪያ ተከልክለው በህወሃት ከባድ መሳሪያ በጅምላ ባላለቁ ነበር። እውነቱ ይኼ ነው፦ መከላከያው የቆመው ከጠቅላይ ሚንስትሩ ጎን ነው፤ ጠቅላይ ሚንስትሩም የቆሙት … ከሚፈሩት “ነገ ከህወሃት ነጥዬ ጎኔ አቆመዋለሁ” ከሚሉት አፍቃሪ–ትህነግ ጎን ነው።
ይህንን የምለው የኣማራው ደህንነት የጠቅላይ ሚንስትሩ “በጎ ችሮታ” ነው ብዬ በማሰብ አይደለም። ኣማራው ለራሱ እራሱ እንደማያንስ ጠንቅቄ አውቃለሁ። ነገር ግን እንደ ክፉ ዕድል ሆነና “ተላላኪ” እንጂ ተሟጋች መሪ ውጥቶለት አያውቅም። በዛሬይቱ ኢትዮጵያ ኣማራው ክብር አይደለም ክልል አልባ ሆኗል። መንግስት በሚሰራበት ሸፍጥ ከኦሮምያና ቤንሻንጉል አይደለም ከራሱም ክልል በሺህዎች ይፈናቀላል፣ በመቶዎች ይገደላል። ይህ ማህበረሰብ ለደረሰበት ዝቅተኛ ውርደት ግንባር ቀደም ተጠያቂው … የታሪክ እድፍ፣ የዘር ጉድፍ የሆነው ብአዴን ቢሆንም፤ በገጠርም ይሁን በከተማ ላለው ኣማራ ደህንነት ቀሪ ተስፋ ግን መሪ ሳይሆን መሣሪያ ብቻ ነው። ፋኖ ተሰማራ … እንደ ጎቤ – እንደ አዝመራ!